ምክትል ከንቲባ ወ/ሮ አዳነች አቤቤ በምክትል ከንቲባ ማዕረግ የአገልግሎት ሰጪ ተቋማት አስተባባሪው አቶ ጃንጥራር አባይ እና ከሌሎች ከፍተኛ የስራ ሀላፊዎች ጋር በመሆን በለገዳዲ ክፍል ሁለት የከርሰ ምድር ውሃ ልማት ፕሮጀክትን ተዘዋውረው ጎብኝተዋል።
የለገዳዲ ምዕራፍ ሁለት የከርሰ ምድር ውሃ ልማት ፕሮጀክት በ17 ጥልቅ የውሃ ጉድጓዶች 86ሺህ ሜትር ኩብ ውሃ ያመርታል ። ፕሮጀክቱ ከቀጣይ አመት ጥቅምት ወር ጀምሮ የመጠጥ ውሃ ስርጭት አገልግሎት ለህብረተሰቡ ለማድረስ እንዲጀምር በትኩረት እየተሠራ ይገኛል ።
የውሃ ፕሮጀክቱ የምስራቅ ሰሜን አዲስ አበባ በተለይ የካ እና የጉለሌ ክፍለ ከተሞችን የንጹህ መጠጥ ውሃ አቅርቦት ችግርን እንደሚቀርፍ ተገልጿል ።
የለገዳዲ ነባር ፕሮጀክት ጉብኝት አላማ ሲገልፁ ለግድቡ ጥገና ከፍተኛ በጀት የሚጠይቅ መሆኑን በጥናት በመቅረቡ ለውሣኔ ያመች ዘንድ፡ ያለበትን በአካል ለማየት ያለመ ጉብኝት መሆኑን ወ/ሮ አዳነች ገልፀዋል።
ከማለዳ ጀምሮ በነበረው የጉብኝት መርሐ ግብር በለገዳዲ የውሃ ማጣሪያ ግድብ ነባር እና አዳዲስ ፕሮጀክቶችን ያሉበትን ደረጃ ተዘዋውረው የጎበኙ ሲሆን በመቀጠል በአቃቂ እየተገነባ ባለው የከርሠ ምድር ውሃ ፕሮጀክት ጉብኝቱ ቀጥሏል።