የአዲስ አበባ ውሃ እና ፍሳሽ ባለስልጣን የጉለሌ ቅ/ጽ/ቤት በስሩ ካሉ እና ህጋዊ ከሆኑ ሰባት ማህበራ ጋር በመነጋገር በቀላሉ ውሃን መልሶ በመጠቀም እንዲገለገሉ ግንዛቤ በመፍጠር ወደ ስራ ገብቷል ፡፡

በአሁኑ ሰዓትም ሶስቱ ሙሉ በሙሉ መጠቀም የጀመሩ ሲሆን አራቱ ማህበራት ደግሞ በሂደት ላይ ናቸው፡፡

ከነዚህ መካከል በጉለሌ ክ/ከተማ ወረዳ አራት የሚገኝ ሚካኤልና ጓደኞቹ የተሸከርካሪ እጥበት ማህበር አንዱ ነው፤የማህበሩ አባላት የተጠቀሙትን ውሃን ያለ ምንም ኬሚካል ቆሻሻውን በማዝቀጥ ብቻ መልሶ በመጠቀም ሂደት እየተገለገሉ ይገኛሉ፡፡

ማህበሩ ከዚህ ቀደም በወር 310 ሜትር ኪዩብ ይጠቀሙ የነበረ ሲሆን ይህ አሰራር ወደ 120ሜ.ኪ ዝቅ አድርጎታል፡፡

ወጣት ሌላነው ተስፋዬ የማህበሩ አባል ሲሆን አሰራሩ አንዴ የሚጠቀሙትን ውሃ ለ20 ጊዜ መላሰው በመጠቀም ወሃ ከመቆጠብ ባለፈ ከዚህ ቀደም ለውሃ ፍጆታ በወር ይከፍሉት የነበረው ዘጠኝ ሺ (9000) ብር ወጪ ወደ ሶስት ሺ (3000) እንደቀነሰላቸው ተናግሯል፡፡

ለ18 ወረዳዎች አገልግሎት የሚሰጠው በባለስልጣኑ ጉለሌ ቅ/ጽ/ቤት የአካባቢው መልከአ ምድራዊ አቀማመጥ እና የውሃ አቅርቦት እጥረት ተዳምሮ የውሃ ችግር ከሚታይባቸው አካቢዎች አንዱ ነው፡፡

በአካበቢው የተሸከርካሪ ማጠቢያዎችና ሻዎር ቤቶች መብዛታቸው ደግሞ ችግሩን በእንቅርት ላይ ጀሮ ደግፍ አድርጎታል፡፡

ይህንንም ችግር በጥቂቱም ቢሆን ለመፍታት እና የተገኘውን የውሃ ሃብት በቁጠባ ለመጠቀም እንዲቻል ምንም አይነት ኬሚካል ጥቅም ላይ ሳይውል ስራው እንዲሰራ መደረጉን የተናገሩት በቅ/ጽ/ቤቱ የውሃ ምርትና ስርጭት ክፍል ሃላፊ አቶ ዉብሸት አልማው፤ ይህም ተግባር አለአግባብ የሚባክነውን ውሃ በማስቀረት ትልቅ አስተዋጽኦ ያበረከተ እና ወደ ሌሎች ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች መስፋፋት ያለበት መሆኑን አስረድተዋል ፡፡