የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን ከ2007 ዓ.ም ጀምሮ ዕንቅስቃሴ በሚበዛባቸው በተለያዩ የከተማዋ ቁልፍ ቦታዎች ያስገነባቸው የመንገድ ዳር ማርፊያ እና የንጽህና መጠበቂያዎች አገልግሎት እየሰጡ መሆናቸው ይታወቃል፡፡

እነዚህን የመንገድ ዳር ማርፊያ እና የንጽህና መጠበቂያዎች ከጊዜ ጊዜ እንዲስፋፉ ለማድረግ ያላሰለሰ ጥረት እየተደረገ ሲሆን በያዝነው በጀት ዓመትም ባለስልጣኑ ባወጣው ዕቅድ መሰረት የተለያዩ ተግባራት በመከናወን ላይ እንደሚገኙ አቶ ደረጄ እንዳልካቸው የመ/ጸ/መ/ጥ/ማ/ን/የስራ ሂደት መሪ ገልፀዋል፡፡

ኃላፊው እንደገለጹት በበጀት አመቱ ተግባራዊ ከሆኑት መካከል ለአብነት ያህል 146 ተንቀሳቃሽ መፀዳጃ ቤቶች፣ 27 ተንቀሳቃሽ የህዝብ ንፅህና መጠበቂያ ግንባታን እንዲሁም 114 የዲዛይን ስራ እና በማህበራት አማካይነት በሶስተኛ ወገን በመረከብ የዋጋ ድርድርና የዕጣ ማውጣት ስራ ተከናውኗል፡፡

በመጻዳጃ ቤት ግንባታ ስራ እና ግንባታው ተጠናቆ ሲተላለፍ የማስተዳደር ኃላፊነቱን በጥቃቅንና አነስተኛ ለተደራጁ ስራ አጥ ወጣቶች እንዲሰጥ በማድረግም በዘርፉ በሁለት መንገድ የስራ ዕድል ተፈጥሯል፡፡

ይህ በእንዲህ እንዳለ በቀጣይ አዳዲስ የመጻዳጃ ቤቶች ግንባታን ባለስልጣኑ አርንጓዴ ተፋሰስ መስሪያ ቤት በማስረከብ የግንባታም ሆነ የማስተዳደር ይሰራል ብለዋል::

በበጀት አመቱ ከተከናወኑ አበይት ተግባራት መካከል የተጠቀሱት ተግባራት እንዳሉ ሆነው ከመሬት አቅርቦት በተያያዘ በተለይም የህዝብ እና ተንቀሳቃሽ መጻዳጃ ቤቶችን ለማስገንባት በዋናነት ቦታ ያለማግኘት ችግር እንዳጋጣማቸው የስራ ሂደት መሪው ጠቁመው ከወሰን ማስከበርም አንፃር እንዲሁ ክፍተት ስለነበር መዘግየቶች ተስተውሏል ብለዋል፡፡

በሌላ በኩል በጥቃቅን ተደራጅተው ወደ ትግበራ እንዲገቡ ከተደረገ በኋላ ዕድሉ የተፈጠረላቸው ምሩቃን ለስራው አዲስ ከመሆናቸው የተነሳ የልምድ እና የአቅም ማነስ ተስተውሎባቸዋል፡፡ በዚህም ምክንያት በተቀመጠው ጊዜ ገደብ እና በሚፈለገው ጥራት ሰርቶ የማስረከብ ክፍተት እንደነበር  የስራ ሂደት  መሪው አቶ ደረጄ እንዳልካቸው ጠቁመዋል፡፡