ዘመናዊ የቆጣሪ ንባብ ስርዓቱ ተግባራዊ የተደረገው በባለስልጣኑ የአራዳ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ስር ባሉ 18 ወረዳዎች ሲሆን በጥቅሉ 47000 (አርባ ሰባት ሺህ ) ደንበኞች ላይ ነው፡፡

ዘመናዊ የቆጣሪ ንባብ ስርአቱ የቆጣሪ ጥራት ችግርን እና ግምታዊ አሞላልን ከማስቀረት ባለፈ ደንበኛው የውሃ ፍጆታውን በተጠቀመበት ወር ለመክፈል ያስችለዋል ፤ ከዚህም ባለፈ የገቢ አሰባሰብ ስርአቱን ከማሳለጥ አንጻር ከፍተኛ ሚና ይኖረዋል ፡፡

የንባብ ስርዓቱ ለዚሁ ተግባር ተብሎ አፕልኬሽን በተጫነባቸው የሞባይል ስልኮች አማኝነት የሚሰራ ሲሆን ቆጣሪ አንባቢው በደንበኛው ቤት ወይም ድርጅት በሁለት ሜትር ክልል ውስጥ ካተገኘ በስተቀር ሲስተሙ አያነብለትም፤ ይህም በስፍራ ተገኝቶ ትክክለኛ መረጃ እንዲያስገባ ያስገድደዋል፡፡

የባለስልጣኑ የደንበኞች አገልግሎት ዘርፍ ምክትል ስራ አስኪያጅ አቶ ሞገስ አርጋው በጉዳዩ ላይ ዛሬ በሰጡት መግለጫ ይህ ዘመናዊ የቆጣሪ ንባብ ስርዓት ተግባራዊ የተደረገው በአራዳ ቅርንጫፍ ጽ/ቤት ስር በሚገኙ አራዳ ክ/ከ ወረዳ 1፣8፣9፣10፤ አዲስ ከተማ ክ/ከ ከወረዳ 1እስከ 4 (በከፊል) ፤ቂርቆስ ወረዳ 7እና 8 ፤ልደታ ክ/ከ ከወረዳ 3 እስከ 9 እና በየካ ክ/ከ ወረዳ 6 ብቻ እንደሆነ ገልጸዋል ፡፡

ተግባዊ የተደረገባቸው ደንበኞችም እስካሁን ያለውን የቆጣሪ ንባብ አሰባሰብና የቢል ዝግጅትን አሰራር ከሲስተሙ ጋር አጣጥሞ ለማስኬድ እንዲያስችል የህዳር እና የታህሳስ ወር ክፍያ በአንድ ጊዜ እንደሚፈጸም አውቀው ክፍያውን ከታህሳስ 26 እስከ ጥር 18 ባለው ጊዜ ውስጥ መክፈል እንዳለባችሁ አሳስበዋል፡፡

በቀጣይም በቀሩት ቅርንጫፍ ጽ/ቤቶች በሚገኙ የባለስልጣኑ ደንበኞች ላይ ተግባራዊ የሚደረግ ይሆናል ፡፡