የኘሮጀክቱ ሥም፡    ለኮዬ ፍጪ ኮንደሚኒየም ቤቶች የውኃ አቅርቦት ልማት ፕሮጀክት

አስፈፃሚው አካል፡-      በአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን የኘሮጀክት ጽ/ቤት

ኘሮጀክቱ የሚገኝበት አድራሻ፡-በአዲስ አበባ ከተማ አቃቂ ኮዬ ፍጪ አካባቢ

ኘሮጀክቱ ጠቅላላ ዓላማ፡- ጉድጓዶቹን በመቆፈርና ወደ ሲስተም በማስገባት በአካባቢው ለሚገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የንጹህ መጠጥ ውኃ አገልግሎት ተጠቃሚ ማድረግ ነው፡፡

የኘሮጀክት አጠቃላይ ግብ፡-በኮዬ ፍጬ አካባቢ ለሚገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የጉድጓድ ቁፋሮ፣ የመስመር ዝርጋታና ተያያዥ የሲቪል ሥራዎች በማከናወን የንጹህ መጠጥ ውኃ አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ይደረጋል፡፡

በኘሮጀክቱ የሚከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት፡-

  • የስርጭት (Transmission Line) መስመር እና የኤሌክትሮ ሜካኒካል ጥናት ማካሄድ፣
  • የጉድጓድ ቁፋሮ ሥራ፣
  • የኤሌክትሮ ሜካኒካል ስራዎች የዕቃ ግዥና ግንባታ፣
  • የቧንቧና መገጣጠሚያ እንዲሁም የተንቀሳቃሽ ውኃ ማጠራቀሚያ ጋን ግዥ፣
  • የማጠራቀሚያ ጋን እና ሌሎች አስፈላጊ የህንጻ ግንባታ ሥራዎች፣
  • የዋና መስመር እና የሥርጭት መስመር ዝርጋታ ሥራ፣
  • የፓምፕና ጥበቃ ቤት ግንባታ እንዲሁም የትራንስፎርመር ተከላ ሥራ
  • የግንባታ ሱፐርቪዥን ሥራ
  • የመዳረሻ መንገድ ግንባታ

ኘሮጀክቱ የተጀመረበት ጊዜ፡-

  • በ2006 ዓ.ም.

ኘሮጀክቱ የሚጠናቀቅበት ጊዜ፡-

  • በ2009 ዓ.ም.

የኘሮጀክቱ ጠቅላላ በጀት፡- 2,000,000,000 ሚሊየን ብር ገደማ ይፈጃል ተብሎ ይጠበቃል፡፡

መግቢያ

በከተማ አስተዳደሩ በአዲስ አበባ ከተማ የሚታየውን የቤት ችግር ለመቅረፍ በተለያዩ አካባቢዎች የጋራ መኖሪያ ቤቶች በመገንባት ላይ ይገኛል፡፡ ከነዚህ ከተጠቀሱ አካባቢዎች የኮዬ ፍጪ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ሥራ አንዱ ነው፡፡ በዚህ በተጠቀሰው አካባቢ ከ60 ሺህ በላይ የሚደርሱ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ለመገንባት በ2006 በጀት ዓመት የመሠረት ድንጋይ የተጣለ ሲሆን አጠቃላይ ግንባታውም እስከ 2007-09 በጀት ዓመት እንደሚጠናቀቅም ተገምቷል፡፡

በዚህ መነሻነት የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለሥልጣን ለግንባታው የሚሆን ውኃ ለማቅረብም ሆነ ግንባታው ከተጠናቀቀ በኋላ በቤቶቹ ለሚኖሩ የህብረተሰብ ክፍሎች የንጹህ መጠጥ ውኃ አገልግሎት ተጠቃሚ ለማድረግ በአካባቢው በአፋጣኝ በመግባት ከ2006 በጀት ዓመት ጀምሮ የተለያዩ ሥራዎችን በማከናወን ላይ ይገኛል፡፡ በዚህም የተለያዩ ጉድጓዶች ቁፋሮ እና የውኃ መስመር እንዲሁም ተያያዥ የሲቪል ሥራዎች እየተከናወኑ የሚገኝ ሲሆን ጉድጓዶቹ በ2007-09 በጀት ዓመት ምርታቸውን በቀጥታ የነባር ማጠራቀሚያዎች አልያም አዲስ ወደ ሚገቡ ማጠራቀሚያዎች የሚሰባሰቡ ይሆናል፡፡ የኘሮጀክቱ ሥራ ተጠናቆ ውሃው ወደ ተዘጋጀለት ማጠራቀሚያ ሲገባ በምርት ከ50,000 በላይ የጋራ መኖሪያ ቤቶች ውስጥ ለሚገቡ የህብረተሰብ ክፍሎቹ  የንፁህ መጠጥ ውኃ ተጠቃሚ እንዲሆኑ የሚያስችል ይሆናል፡፡

የኘሮጀክቱ አስፈላጊነት

የአዲስ አበባ ሕዝብን የእለት ተእለት የመኖሪያ ቤት ዕጥረት ቀስ በቀስ ለመፍታትና ወደ ተሻለ ደረጃ ለማሣደግ መንግሥት ከፍተኛ መዋለ ንዋይ እያፈሰሰ ይገኛል፡፡ በመሆኑም ከነዚህ ቤቶች ግንባታ ጎን ለጎን የመሠረተ ልማት ማሟላት አንዱና ዋነኛው ጉዳይ በመሆኑ የዚህ ፕሮጀክት መቀረጽ ለግንባውም ሆነ ግንባታው ከተጠናቀቀ በኋላ ለሚሰፍሩ የህብረተሰብ ክፍሎች የንጹህ መጠጥ ውኃ ለማቅረብ የሚኖረው አስተዋፅኦ የጎላ ይሆናል፡፡

የኘሮጀክቱ ዓላማ

የዚህ ፕሮጀክት ዋነኛ ዓላማ በኮዬ ፍጬ አካባቢ ለሚገነቡ ከ65,000 በላይ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የንፁህ መጠጥ ውኃ ማቅረብ ነው፡፡

የኘሮጀክቱ ግብ

በኮዬ ፍጬ አካባቢ ለሚገነቡ የጋራ መኖሪያ ቤቶች የጉድጓድ ቁፋሮ፣ የመስመር ዝርጋታና ተያያዥ የሲቪል ሥራዎች በማከናወን የንጹህ መጠጥ ውኃ አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆኑ ይደረጋል፡፡

የሚጠበቅ ውጤትና ተጠቃሚዎች

 በከተማዋ ለሚካሄደው የጋራ መኖሪያ ቤቶች ግንባታ ሥራ ጋር ተያይዞ የጋራ መኖሪያ ቤት ተጠቃሚ ለሚሆኑ የከተማዋ ነዋሪዎች የንጹህ መጠጥ ውኃ አገልግሎት ተጠቃሚ እንዲሆኑ በማስቻል ነዋሪዎች በወቅቱ ከውኃ አንጻር መሠረተ ልማቱ የተሟላ መኖሪያ ቤት በወቅቱ እንዲያገኙ የሚያስችል ይሆናል

 በ2008 በጀት ዓመት የሚከናወኑ ዋና ዋና ተግባራት

  • ከ9 ጥልቅ ጉድጓዶች መካከል የቀሪ 2 ጉድጓዶች ቁፋሮ ሥራ ማጠናቀቅ፣
  • ኤልሲ እስከ ሐምሌ ወር ማብቂያ በማስከፍት የ8 ኪ.ሜ. ዋና፣ 24 ኪ.ሜ የስርጭት እና የ7.4 ኪ.ሜ. ማሰባሰቢያ መስመር ዕቃ አቅርቦት ሥራ ማከናወን
  • ከ8 ኪ.ሜ. ውስጥ 7 ኪ.ሜ. የዋና፣ ከ24 ኪ.ሜ ውስጥ 22 ኪ.ሜ. የስርጭት እና ከ7.4 ኪ.ሜ. ውስጥ የ6.7 ኪ.ሜ. የማሰባሰቢያ መስመር ዝርጋታ ሥራ ማከናወን
  • ከጉድጓዶች እና ግፊት መስጫ ጣቢያዎች ጋር ተያያዥ የሆኑ የሲቪል ሥራዎች እንዲሁም የመዳረሻ መንግድ ግንባታ ሥራ ማጠናቀቅ፣
  • የኤሌክትሮሜካኒካል ዕቃ አቅርቦትና ተከላ ሥራ ማጠናቀቅ፣
  • የግንባታ ቁጥጥር ሥራ ማከናወን፣
  • ለተቆፈሩ የውኃ ጉድጓዶች የኤሌክትሪክ ኃይል ማስገባት፣
  • የመያዥያ ክፍያ መፈጸም (ለ4 ጉድጓዶች)፣
  • የወሰን ማስከበር ሥራ ማከናወን፣

የአፈጻጸም ስልቶች 

የውኃ አቅርቦቱ ሥራ በታለመለት ጊዜ ውስጥ እንዲጠናቀቅ ለማድረግ የሚከተሉት የአፈጻጸም ስልቶች አስፈላጊ ይሆናሉ፡፡

  • በቁፋሮ ሥራ፣ በመስመር ዝርጋታ እና ተያያዥ ሥራዎች የሚሳተፉ ተቋራጮች የሚያቀርቡትን ሰነድ መገምገም፣
  • ለቁፋሮ፣ ለመስመር ዝርጋታና ተያያዥ የሲቪል ሥራዎች የሚመረጡ ተቋራጮችን መቆጣጠር፣
  • የሥራ ሣምንታዊና መርሃዊ ሪፖርቶችን መቆጣጠርና መገምገም፣

 

የአካባቢና ማህበራዊ ትንታኔ

አጠቃላይ የውኃ አቅርቦት ሥራው በአብዛኛው በማህበራዊ ጉዳይ የሚኖራቸው አሉታዊ ተጽዕኖ ከቦታ ይገባኛል ጥያቄ እና ከካሣ ክፍያ ጋር የተያያዘ ስለሆነ በአካባቢያቸው የሚገኘው ቀበሌና ክ/ከተማ የግንዛቤ ማስጨበጫ ሥራ መስራት ይገባቸዋል፡፡ በሥራው በተለይ የጉድጓዶቹን አካባቢ ነዋሪ የመጀመሪያ ተጠቃሚ ስለሚያደርገው ችግሩን ለማቅለል ይሞከራል፡፡

የክትትልና የግምገማ ስርዓት

 የሚሰሩትን ዝርዝር ሥራዎች ለመቆጣጠር የተዘረዘሩትን የክትትል የግምገማ ሥርዓቶች መካከል፣

ሀ/    ለቁፋሮ ሥራ፣ በመስመር ዝርጋታ እና ተያያዥ ሥራዎች የሚመረጡ የሀገር ውስጥ ተቋራጮች በሚያስገቡት ሰነድ ከፍላጐት ጋርና የገበያውን ሁኔታ ባገናዘበ መልኩ መሆኑ ይመዘናል፣

ለ/    ሥራዎች በሚከናወኑበት ወቅት ከኘሮጀክት ቢሮው በተመደቡ ባለሙያዎች ለሥራዎቹ ጥራትና መስፈርት በተዘጋጀው ውለታ መሠረት ይታያሉ፣

ሐ/    ለተሰሩት ሥራዎች የሚቀርቡ ማናቸውም ክፍያዎች በቅድሚያ በሚደረጉ ማጣራቶች ተመዝነው ክፍያቸው የሚፈፀምበት ሥርዓት ይተገበራል፣

 ስጋትና ምቹ ሁኔታዎች

 የኘሮጀክቱ ሥራ በታሰበለት ፍጥነትና በታሰበበት የጊዜ ገደብ ለመወጣት ስጋት ሆነው የሚቀጥሎ ጉዳዮች፡

  • ለሥራዎቹ የሚሆኑ ግብዓቶች በታሰበላቸው የጊዜ ገደብ አለመገኘት፣
  • የይዞታ ይገባኛል ጥያቄ ችግር፣

ምቹ ሁኔታዎች

  • የውሃ ጥያቄ ከፍተኛ መሆን፣

በጀት

  • በ2008 በጀት ዓመት ለሚሰሩ ሥራዎች ወጪ በአጠቃላይ 341,946,050 ብር በላይ የሚያስፈልግ ይሆናል፡፡
ተ.ቁ. የፕሮጀክቱ ሥምና የሚከናወኑ ዝርዝር ተግባራት የውል ስምምነቱ መጠን/ኢንጂነሪግ ዋጋ ግምት ለ2008 በጀት ዓመት የተያዘ በጀት የተያዘ በጀት ምርመራ
ከመንግስት ከመ/ቤቱ ከብድር ዕርዳታ
1 ኮዬ ፍቼ ቅሊንቶ እና ቱሉ ዲምቱ አካባቢ የውኃ አቅርቦት ልማት ፕሮጀክት   341,946,050 341,946,050 0 0 0
1.1 የተቋራጭ ቅጥር በመፈጸም ከጉድጓዶች እስከ ማጠራቀሚያ የመስመር ዕቃ አቅርቦት፣ ዝርጋታና ተያያዥ የሲቪል ሥራዎች ማከናወን 286,590,000 100,000,000 100,000,000 በተገባው ውለታ መሠረት ለዕቃ አቅርቦቱና በ2008 በጀት ዓመት ለሚሰሩ ሥራዎች ማስፈጻሚያ በጀቱ ተይዟል፡፡አጠቀላይ ሥራው የ9 ወር ውለታ ቢሆንም ከሥራው ባህሪ አንጻር ወደ 12 ወር ተራዝሞ ተይዟል፡፡
1.2 የተቋራጭ ቅጥር በመፈጸም ከማጠራቀሚያ እስከ ሥርጭት የመስመር ዕቃ አቅርቦት፣ ዝርጋታና ተያያዥ የሲቪል ሥራዎች ማከናወን 286,590,000 100,000,000 100,000,000
1.3 የተቋራጭ ቅጥር በመፈጸም የኤሌክትሮ ሜካኒካል ዕቃ አቅርቦትና ተከላ ሥራ ማከናወን 197,046,000 100,000,000 100,000,000
1.4 የግንባታ ቁጥጥር ሥራ ማከናወን 3,921,050 3,921,050 3,921,050 ከግንባታ ሥራው ጋር በተያያዘ በ2008 በጀት ዓመት ለሚከፈል የአማካሪ ክፍያ በጀት ነው፡፡
1.5 ለተቆፈሩ የውኃ ጉድጓዶች የኤሌክትሪክ ኃይል ማስገባት 9,600,000 9,600,000 9,600,000 ከዚህ ቀደም ለ70ሺህ ውኃ አቅርቦት ለጉድጓድ ትራነስፎርመር አቅርቦት የተያዘውን በጀት መነሻ በማድረግ በዚህ ፕሮጀክት ለተቆፈሩ 9 ጉድጓዶች ትራንሰፎርመር አቅርቦት በጀቱ ተይዟል፡፡
1.6 የ2 ጉድጓድ ቁፋሮ ክፍያ እና የመያዥያ ክፍያ መፈጸም (ከ4 ጉድጓዶች ጋር በተያያዘ) 37,069,457 21,000,000 21,000,000 በተገባው ውል ስምምነት መሠረት ከሌን ሥራ ተቋራጭ ጋር በተያያዘ ለሚከፈል የ2 ጉድጓዶች ዋጋ እንዲሁም ለ4 ጉድጓዶች ለሚከፈል የመያዥያ ክፍያ በጀቱ ተይዟል፡፡
1.7 የካሳ ክፍያ መፈጸም 7,425,000 7,425,000 7,425,000 ከፕሮጀክቱ ትግበራ ጋር በተያያዘ ለሚከፍል ካሳ ክፍያ የተያዘ በጀት ነው፡፡