የአዲስ አበባ ውሃና ፍሳሽ ባለስልጣን በ2012 በጀት ዓመት በከፍተኛ እና መለስተኛ የፍሳሽ መስመሮች ላይ የገጠማቸውን 472 የፍሳሽ መስመር ክዳን (ማንሆል) ተሰርቋል፡፡

ከተሰረቁት ማንሆሎች 321 የሚሆኑት የብረት ክዳኖች ሲሆኑ 151ዱ ደግሞ የኮንክሪት ክዳኖች ናቸው፡፡ እነዚህ ክዳኖች በገንዘብ ሲተመኑም 4 ሚሊዮን 794 ሺህ ብር በላይ የወጣባቸው ናቸው፡፡

በማንሆል ስርቆት ምክንያት ወደ ፍሳሽ መስመር በሚገቡ ጠጣር እና ባዕድ ነገሮች የፍሳሽ አወጋገድ ስርዓቱ እየተስተጓጎለ ከመሆኑም በላይ ተከድነው የነበሩ ማንሆሎች ክፍት ስለሚሆኑ በሰው እና በእንስሳት ላይ ሳይጠበቅ ጉዳት እያጋጠመ ይገኛል፡፡

በስርቆት ምክንያት እየጠፋ ያለው ሃብት የህዝብ እና የሃገር ንብረት በመሆኑ ህብረተሰቡ በአከባቢው የሚገኙ የፍሳሽ መስመር ክዳኖችን በመጠበቅ እና ድርጊቱን በመፈፀም ላይ የሚገኙ አካላትን በመጠቆም የበኩሉን አስተዋፅኦ እንዲወጣ ባለስልጣኑ ጥሪውን ያስተላልፋል፡፡